የክልሉ ሲቪል ሰርቪስ ቢሮ ከተለያዩ ተቋማት ጋር የአቅም ግንባታ የትብብር ስምምነት ተፈራረመ
*************
(አሶሳ፣ሐምሌ 7/2018 ዓ.ም) የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሲቪል ሰርቪስ ቢሮ የአቅም ግንባታ ሥራዎችን ለማጠናከር የሚያስችል የትብብር መግባቢያ ስምምነት ከተለያዩ ተቋማት ጋር ተፈራርሟል።
የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር እና የሲቪል ሰርቪስ ቢሮ ኃላፊ አቶ አቶ ጌታሁን አብዲሳ የመግባቢያ ስምምነቱን ከአሶሳ ዩኒቨርሲቲ፣ ከአሶሳ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ እና ከክልሉ ብቃትና ስራ አመራር ተቋም ጋራ ዛሬ ተፈራርመዋል።
የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር እና የሲቪል ሰርቪስ ቢሮ ኃላፊ አቶ ጌታሁን አብዲሳ በዚሁ ወቅት፣ ዜጎችን ማዕከል ያደረገ አገልግሎት አሰጣጥን እውን ለማድረግ ተቋማትን ወደ ሪፎርም ትግበራ የማስገባት ሥራ እየተሠራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
በመጀመሪያ ምዕራፉ 8 የመንግስት ተቋማት የሪፎርም ትግበራ ምዕራፍ እንዲካተቱ በማድረግ ዜጎች ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲያገኙ ጥረት እየተደረገ መሆኑንም አቶ ጌታሁን ጠቁመዋል።
ከተለያዩ ተቋማት ጋር የተደረገው የትብብር ስምምነት የሰው ኃይል ክህሎትን ለማብቃትና ጠንካራ ተቋማዊ የሆነ የቅንጅት ስርዓትን ለመዘርጋት ያለመ ነው ብለዋል።
ለአቅም ግንባታና የሪፎርም ስራዎችን ውጤታማ ለማድረግ አቅም መገንቢያ ተቋማት ድርሻቸው የጎላ እንደሆነም አቶ ጌታሁን ገልጸዋል።
ስምምነቱ የሲቪል ሰርቪሱን የዲጂታላይዜሽንና የቴክኖሎጂ ሽግግር ፍላጎትን ለመደገፍ የሚያስችል ተግባር ተኮር ስልጠናዎችን ለማጠናከር ትልቅ ፋይዳ እንዳለው አስረድተዋል።
በስምምነቱም ተቋማቱ በክልሉ የሲቪል ሰርቪስ የአሰራር፣ የመዋቅርና የገልግሎት አሰጣጥ ተግዳሮች ዙሪያ ችግር ፈቺ ሳይንሳዊ ጥናትና ምርምሮችን ያካሂዳሉ ተብሏል።
የክልሉ ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች ብሎም ለሰራተኞች ብቃት ክፍተት መሰረት በማድረግ አጫጭርና ረጃጅም ስትራቴጂክ የአቅም ግንባታ የአመራር ጥበብ ስልጠናዎችን ለመስጠት ተቋማት ተቀራርበው እንደሚሰሩም በስምምነቱ ወቅት መግባባት ላይ ተደርሷል።
ዘገባው#የቤኒሻንጉል_ጉሙዝ_ክልል_የመንግሥት_ኮሙኒኬሽን_ጉዳዮች_ቢሮ ነው
News
በሲቪል ሰርቪስ ቢሮ እና የአቅም መገንባያ ተቋማት ጋር የጋራ የትብብር ስምምነት ተፈራረመ